Komentar baru

Advertisement

መነሳንስ

Eriyot Alemu
Dec 26, 2016
Last Updated 2023-08-21T04:16:42Z
Advertisement




ምዕራፍ አንድ
አያትነት። የልጅ ልጅ ማየት። የምር አያት ሳይሆኑ የተምሳሌት አያት መሆን—መስከን። ከወዲሁም ራስን በአያትነት ቦታ ላይ ቁጭ አድርጎ፣ የሚቀሩትን ጥቂት የመቆያ ጊዜያት እያሰቡ፣ በትዝታና በአስተውሎት ቅኝቶች እየተንጎማለሉ ቀን መግፋት። በርጋታ ባህር ውስጥ ሙሉ በሙሉ በመስጠም፣  ራስን በአያትነት ቦታ ላይ ቁጭ አድርጎ፣ የጊዜ ወንዝ– በልጆች እና ልጅ ልጆች ላይ የሚያመጣውንና ይዞ የሄደውን ነገር የሚያስተውሉበት ወቅት ነው— ዩንቨርስቲ ሶስተኛ አመት። 

ይሄ ዓመት:— ፍሬሽነት ላይ ከነበረው ሁሉን በእኩል አይን እያየ፣ ማንንም ከማንም ሳያስበልጥ፣ ጠፍሮ ከሚያስር የፍራቻ ስሜት የሚላቁበት ዓመት ነው። አዲስነት ከሚፈጥረው የበታችነትና ያላዋቂነት ስሜት ሙሉ በሙሉ ነፃ የሚሆኑበት ዓመትም ነው።

ይሄ ዓመት:— ሁለተኛ አመት ላይ ከሚፈጠር፣ መቼም ቢሆን ሊፋቱት ከማይችል ከሚመስል፣ በከፊል ፍራቻና በከፊል ነፃ መሆን መሃል ላይ ካለ፣ የትግል ስሜት የሚፋቱበት አመት ነው። ልክ በሁለቱም በኩል በተሳለ ቢላዋ፣ በሁለቱም በኩል ለመቆረጥ ዝግጁ በመሆን፣ ወይ ሽክትፍፍ ብሎ ተቆራርጦ ለማለቅ አልያም ለቀጣይ ህይወት በአግባቡ ተቀርፆ ለመቀጠል፣ አዲስን ነገር በድፍረት ለማድረግ፣ ለማንም ባልተከለከለው የህይወት መሮጫ መም ላይ ለመግባት፣ ከሚጣደፉበት ሩጫ የሚላቀቁበት አመት ነው። ከተጋነነ ልበ ሙሉነትና "ከኔ በላይ ማን አለ?" ከሚል የመንጠራራትም ስሜት ነፃ የሚወጡበት አመት ነው—የዩንቨርስቲ ሶስተኛ አመት።
                            ***
የመጀመሪያውን አመት ‘ፍሬሽነቱን’ ሙሉ በሙሉ ብቻውን ነው ያሳለፈው። ሰው የሚገናኘው በትምህርት ክፍለ ጊዜው ብቻ ነበር። ይሄም ሰው ማግኘት ከተባለ ነው። ለነገሩ ከሰው ጋር የሚቀላቀለው ቢባል የተሻለ ሳይገልፀው አይቀርም።

ሁለተኛ አመቱን  ደግሞ አልፎ አልፎ ቤቱ ከሚመጣውና (እሱ ፈልጎት ተዋውቆት፣ አጋጣሚ እንዳስተዋወቀው ከሚያስመስለው) ብቸኛ ጓደኛው ጋር ከሚያሳልፈው ጊዜ በቀር፣ ይሄንንም አመት በአብዛኛው ብቻውን ነው ያሳላፈው።

አሁን ሦስተኛ አመቱ ላይ ደርሶ አያት ሆኗል። በዚህ አመቱ ከብቸኛ ጓደኛው በተጨማሪ በዩንቨርስቲው ውስጥ እንደ ቡድን ከሚንቀሳቀሱ በዛ ያሉ ግሩፖች መሃል አንዱን ለመቀላቀል ዝግጅቱን ጨርሷል።

አንድም የባከነች ቀን ኖራው አታውቅም። ስለወደፊቱም አሁን ላይ ቆሞ መናገር ቢከብድም እንደ አኳሃኑ ግን በዚሁ የሚቀጥል ይመስላል። ትምርቱን እንደ መሸጋገሪያ ድልድይ እንጂ አንድም ቀን "ዋናዬ" ብሎ አስቦት አያውቅም። ይሄ ለሱ ትርፉ ነው። ሌሎች እጅግ ብዙ ስራዎች አሉብኝ ብሎ ያስባል። እነዚህን ስራዎቹን "ወድጄ፣ ፈቅጄ፣ በጉብዝናዬ ወራት ባለው ጫንቃዬ ላይ ልሸከማቸው የሚገቡኝ ናቸው" ይላል ብዙ ጊዜ ለራሱ።

በጣም ታታሪ ሰራተኛ ነው።አንድን ነገር ባሰበው ጊዜ ሰርቶ ሲጨርስ የሚጎናፀፈው የእርካታ ስሜት፣ ለነገ እድሜው መቀጠል "እንደ ዋስትና" ሆኖ ስለሚታየው፣ ምንም አይነት ስራ ሲሰራ መሰላቸት አይታይበትም። እንደውም የሚሰራ ሁሉ አይመስልም ቢባል ሳይሻል አይቀርም። ሆኖም እንደ መንጠላጠያ መሰላል አርጎ የሚያስበውንም ትምህርቱን ሙሉ ፊቱን አልነፈገውም። ብዙ ነገርን አብሮ ማስኬድን ተክኖታል።

በሶስተኛ አመቱ ባለው ዛሬ ቀንም፣ አንደኛ እና ሁለተኛ አመቱ ላይ እያለ የኖረበት ቤት ውስጥ ነው ያለው። መስኮት የሌለው ቤት ውስጥ። ግን ዛሬ ቤቱን ልብ ብሎ እያየው ነው። ምናልባት ሁሉ ነገር መስመር እየያዘለት ስለሆነና አሁን ለጊዜው የሚሰራው ስላጣ ይሆናል።

ሁሌም የሚሰራው ስራ ሲያጣ እንደሚያደርገው ግንባሩን በመዳፉ መታ መታ እያረገ "ለምን ግን መስኮት አልሰሩለትም?" እንዳለ ጓደኛው ትዝ አለው። "መስኮት የቤት አፍንጫ ነው" ብሎት ነበር። "ሰው ያለ አፍንጫ እንዲኖር ሆኖ አልተፈጠረም። ቤት ግን ያለ አፍንጫ መኖር እንደሚችል ይሄ ቤት ማሳያ ነው" ብሎ ለራሱ መለሰና እንደገና ቤቱን ከዳር እስከዳር ቃኘው። እንኳን እፍኝ ለምታክል መስኮት አይደለም ሌላ ሶስት አራት በር የሚያቆም ሰፊ ቦታ አለው—ቤቱ።

ሁሌም ቤቱን ባሰበ ቁጥር ጓደኛው ትዝ ይለዋል። ለመጀመሪያ ጊዜ ቤቱን ያየው ለት፣ ቤቱን ከስሩ እንደ ውሃ ልክ የተቆለለ አፈር ስለከበበው
"ቆይ እኔ ምልህ, ,, የዚ ቤት ቤተሰሪዎች ምስጦች ናቸው እንዴ? እውነት ለመናገር ይሄን ያረጀ አፈር የመሰለ ጣሪያውንም ጨምረህ ስታይ፣ ሰው የሰራው ቤት ሳይሆን እንዲሁ በምስጦች ተጀምሮ ለምስጦች የተሰራ ቤት ይመስላል,,,, ለዛም ነው እዚህ ቤት ስመጣ፣ ውስጤ ምስጥ የማይበላው ፌስታል ጫማህን አርገህ ሂድ ያለኝ" ብሎ እየሳቀ እግሮቹ ያጠለቁትን ሸበጥ ጫማውን በእጁ አሳይቶት ነበር።

"ወይንስ ከቅዱስ ላሊበላ ጋር ፉክክር መያዛቸው ነው። አንድ ላይ ድንገት ተቆልሎ በተገኘ አፈር ቦርቡረው ቤት መስራታቸው? ,,  አቤቱ! አንተ መሃት፣ መቅሰፍት ይበላሃል እያሉ እንደሞያስፈራሩን ሰባኪዎቻችን እንዳይደለህ አውቃለው። አንተ ቀልድ አዋቂ ነህ!!! መቼስ ያ ርኩስ ፍጥረትህ ኩመካ ላይ እምብዛም ነው። ቀልድስ ያንተ ጥበብ ፍሬ አይደለምን?" እያለ እጆቹን ወደ ሰማይ ቀስሮ ያንጋጥና እየሳቀ

"ለካ ‘እያነቡ እስክስታ’ እንዳለ ሁሉ ‘እየሳቁ ፀሎትም’ እንዳለ የገለፅልክልኝ ጌታ ሆይ,,, እኔ ለቀልድ ታህል እንጂ ለክፋት እንደማልሳፈጥህ፣ ኩላሊትና ልብን የሚመረምረው እውቀትህ ያውቀዋል,,,, ይቅር በለኝ በቃ" ይላል መሬት ተደፍቶ።

የጓደኛውን ነገር ትቶ ከቤቱ ጋር ያጣመረውን ጉዳይ ማሰብ ጀመረ። ብዙ አልቆየም፣ ቤቱን የሚቆልፍበትን ትልቅ ጋን እንዳየ አሁንም ጓደኛው ትዝ ብሎት ፈገግ አለ።
"ቆይ ምን አይነት ወንጀል ብትሰራ ነው እየከፈልክ የምትታሰረው? ሰው እኮ የዋስ መብቱን በገንዘብ የሚያስከብረው፣ ጉዳዩን ከእስር ቤት ውጪ ሆኖ ለመከታተል እንዲያመቸው ነው።"  ብሎት ነበር።
ፈገግታውን ጨመር አረገውና "ካልነገርኩት ማንም አይገባውም! ማንም!!!!!" አለና ብድግ አለ።

ሳምሶን ባህሩ ሲሳይ ራሱ የኔ ለሚለው ነፃነቱ ታጋይ ነው። ማንም ሰው በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ስሜቱን እንዲፈታተነው አይፈቅድም።ሰው በጣም ይወዳል። ግን ብዙ ነገሩን ከሰዎች ጋር መጋራት አይወድም። ለዛም ይመስላል፣ የዩንቨርስቲ ተማሪ ሆኖ ጅማ የመጣ ጊዜ "የተማሪዎች የጋራ መኖሪያ ህንፃ" የሚለው ከስሙ ጀምሮ ያልጣመው።

በሚፈልገው ጊዜና ሁኔታ እንጂ ባልፈለገው ሰዓት ሰዎች እንዲያገኙት አይፈቅድም። ለዛም ነው ብዙ ጊዜ ብቻውን የሚሆነው። ሆኖም ከጥቂት ጊዜያት በቀር የብቸኝነት ስሜት ተሰምቶት አያውቅም። ለዛም ነው አሁንም ሶስተኛ አመቱ ድረስ፣ ከዩንቨርስቲው ውጪ መስኮት የሌለው ቤት ውስጥ ተከራይቶ የኖረው።

ድንገት በጣሪያው ላይ የሚሄድ ነገር ሲሰማው አጀንዳውን ተንደርፍሮ አወጣውና ቁጭ አለ። "ሜኔ ቴቄል ፋሬስ" ብሎ ፅፎ ከመሃል የታጠፈ ነጭ ወረቀት አወጣና አጀንዳውን ዘጋው። ወረቀቱ ላይ በአንዱ ግርጌ ቀን ፃፈበት። በአንዱ ደሞ ደብዳቤ ቁጥር 27/99 ብሎ አሰፈረ።

" ያ ቀን እየመጣ ነው,,,,,," ብሎ መፃፍ እንደጀመረ ስልኩ ጠራ። ተገረመ። ሌላ ጊዜ ቢሆን ሊናደድ ይችል ነበር። ሌላ ጊዜ እንዲህ አይነት ነገር ከመጀመሩ በፊት ስልኩን ያጠፋው ነበር። ከቤተሰቦቹ ውጪ ሊደውልለት የሚችለው አንድ ሰው ነው። እሱም ብቸኛ የግቢ ጓደኛው አቤሴሎም ሃይሌ ነው። ራሱ ነበር,,,,

"ሄሎ"
"ነገ ነው እንዴ?"
"እረፍት ላይ መሆኔን እያወክ!!!"
"ምንም አይደል ጉረኛ"
ስልኩን ዘጋና ዙሪያው ያሉትን ነገሮች አንድ በአንድ ማስተካከል ጀመረ። አቤሴሎም ቤቱ ሊመጣ ነው። ሳይደውልለት ፈፅሞ አይመጣም። በዚ ጉዳይ አውርተው ባያቁም ፍፁም ይግባብሉ።

ነገ ፍሬሽ ተማሪዎች ግቢውን የሚቀላቀሉበት ቀን ነው። አቤሴሎም ደሞ የሚቀበላት ፍሬሽ ጎረቤት አለችው። በዚ ጉዳይ ሊያወራው ነው የሚመጣው።

iklan
Comments
  • Stars Rally to Beat Predators in Winter Classic at Cotton Bowl

Leave Your Comment

Post a Comment

ሱስ ነክ ጉዳዮች

Advertisement